Search
Close this search box.

ግሎባል ባንክ ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት መስጠት ሊጀምር ነው

Share the Post:

ግሎባል ባንክ ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት መስጠት የሚያስችለውን ፈቃድ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የተቀበለ ሲሆን በአጭር ጊዜ ውስጥም ስራ ይጀምራል፡፡

ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት የሸሪዓ የፋይናንስ መርሆችን በመከተል በአገልግሎት ወቅት ምንም አይነት ወለድ መክፈልም ሆነ መቀበል የማይፈቅድ ሲሆን በሸሪዓ በተፈቀዱ ስራዎች ላይ ብቻ የሚሳተፍ የራሱ የሆነ አሰራር ያለው ሆኖ ማንኛውም አገልግሎቱን መጠቀም ለሚፈልግ ደንበኛ የቀረበ አማራጭ የባንክ አገልግሎት ነው፡፡

ግሎባል ባንክም ይህን አገልግሎት እንዲሰጥ ከብሔራዊ ባንክ ፈቃድ ያገኘ ሲሆን አገልግሎቱም በመላው አገሪቱ ተሰራጭተው በሚገኙ የባንኩ ቅርንጫፎች ውስጥ ተለይተው በተሰናዱ መስኮቶች ለመስጠት ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡ በእነዚሀ መስኮቶች የሚፈጸሙ ማናቸውም የገቢ እና የወጪ ሒሳብ እንቅስቃሴዎች ከመደበኛው የባንክ አሰራር ጋር ሳይቀላቀሉ በተለይ ለዚሁ አገልግሎት ተብሎ በተዘጋጀ ቴክኖሎጂ በመታገዝ ይከናወናል፡፡ ባንኩ በተመረጡ ቅርንጫፎቹ ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት መስኮቶችን በመመደብ እንዲሁም በአዲስ አበባ ከተማ እና በክልል አንዳንድ ከተሞች ከወለድ ነጻ የባንክ አገልገሎት ብቻ የሚሰጡ ቅርንጫፎችን ለመክፈት አቅዷል፡፡

ከወለድ ነጻ የባንክ አገልገሎት ብቻ የሚሰጡት ቅርንጫፎች ሙሉ በሙሉ የተጠቃሚዎችን በተለይም የእስልምና ዕምነት ተከታዮችን ምቾት የጠበቁ እንዲሆኑ ማድረግ የሚያስችል አቅርቦት ያሟሉ ሲሆን የእስልምና እምነት ተከታይ ደንበኛ ሀይማኖታዊ ስርዓት ለመከወን ቢፈልጉ የባንኩ የወለድ ነጻ ቅርንጫፍ ንጹህ የመታጠቢያ እና የመስገጃ ቦታዎችን በውስጡ የያዘ በመሆኑ ደንበኞች በነጻነት ቦታዎቹን መጠቀም ይችላሉ፡፡

ባንኩ የተገልጋዩን ህብረተሰብ ልዩ ጥያቄ እና ፍላጎት ለማርካት፣ ተደራሽነቱን ለማስፋት፣ ሁሉን አቀፍ አገልግሎት ለመስጠት እንዲሁም  ትርፋማነቱን ለማሳደግ ሲል ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት ማቅረቡ ተወደዳሪነቱን እና ተመራጭነቱን ይበልጥ ጎለብታል፡፡

ግሎባል ባንክ ለተገልጋዮች ያቀረባቸው አበይት ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት አይነቶች የዋዲያ እና የኢንቨስትመንት ተቀማጭ ሂሳብ አገልግሎት፣ የፋይናንሲንግ አገልግሎት፣ አለም አቀፍ የባንክ አገልግሎት፣ የውጭ ምንዛሬ አገልግሎት፣ የተለያዩ የባንክ ዋስት እና የገንዘብ ማስተላለፍ (ሀዋላ) አገልግሎት ሲሆን እነዚህም በየዘርፋቸው በርካታ ልዩ ልዩ አይነት አገልግሎቶችን ይዘዋል፡፡

ግሎባል ባንክ መደበኛ እና ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎቶችን ከ110 በላይ በሚሆኑ ቅርንጫፎቹ እና ከ1800 በላይ በሆኑ ሰራተኞቹ ለደንበኞች አርኪ አገልግሎት የሚሰጥ ባንክ ሲሆን ከጊዜ ወደ ጊዜም ፈጣንና ከፍተኛ እድገት እያስመዘገበ የመጣ ባንክ ነው፡፡ ባንኩ በአሁኑ ጊዜ የተከፈለ ካፒታሉ ከብር 1.2 ቢሊየን በላይ፤ የተቀማጭ መጠኑ ከ8 ቢሊየን በላይ፤ የብድር መጠኑ ከ7.2 ቢሊየን፣ የሃብት መጠኑ 7.8 ቢሊየን ደርሷል፡፡