
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ለደንበኞች የስኬት መዳረሻ ብርቱ አጋር ሆኖ እንደሚቀጥል የባንኩ ቺፍ ኮርፖሬት ባንኪንግ ኦፊሰር አቶ ሳኅለሚካኤል መኮነን ገለፁ።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ የባንኩን የስራ እንቅስቃሴ ከደንበኞቹ ጋር የሚያስተዋውቅበት “ግሎባል ቱር” የተሰኘውን የውይይት መርሃ ግብር በድሬዳዋ ከተማ ከሚገኙ ደንበኞች ጋር ሐምሌ 10 ቀን 2017 ዓ.ም በኢስት ስታር ሆቴል አከናውኗል።
በተጠናቀቀው የሂሳብ ዓመት በሁሉም መመዘኛዎች አመርቂ ውጤት መመዝገቡን በውይይቱ ወቅት የገለፁት አቶ ሳኅለሚካኤል በቀጣይም ከደንበኞቻችን እና ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር የተጀመረውን የእድገት ጉዞ እናስቀጥላለን ብለዋል።
በውይይቱ የመወያያ ርዕስ ያቀረቡት የደንበኞች ግንኙነት መምሪያ ዳይሬክተር አቶ መሰረት አሰፋ ባንኩ ከተመሰረተበት ጀምሮ ያለውን የዕድገት ለውጥ ምን እንደሚመስል አብራርተዋል።
ከግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ጋር መስራታቸው ለስኬት እንዳበቃቸው የገለፁት የውይይቱ ተሳታፊዎች በቀጣይም ደንበኝነታቸውን ይበልጥ እንደሚያጠናክሩ ተናግረዋል።
ለአንዳንድ የባንክ አገልግሎት አዲስ አበባ ድረስ መሄድ ይጠበቅባቸው እንደነበረ የገለፁት የውይይቱ ተሳታፊዎች የድሬዳዋ ማስተባበሪያ ቢሮ መከፈቱ ጊዜና ገንዘባችንን ከመቆጠብ በተጨማሪ ስራችንን ይበልጥ እያቀላጠፈልን ነው ብለዋል።



ደንበኞች የተለያዩ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን እንዲሁም መስተካከል ይገባል ያሉትን ሀሳብም በመድረኩ አንፀባርቀዋል።
በውይይት መርሃ ግብሩ ከደንበኞች ለተነሱ ጥያቄዎች እና አስተያየቶች ምላሽ የሰጡት አቶ ሳኅለሚካኤል መኮነን ደንበኞች ከባንኩ ጋር ለመስራት ያላቸው ፍላጎት የሚበረታታ መሆኑን አመላክተው ከባንኩ ጋር ለሚሰሩ ደንበኞች ሁለንተናዊ ድጋፍ በማድረግ የስኬታችሁ ብርቱ አጋር መሆናችንን በድጋሜ እናረጋግጣለን ብለዋል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ መላው የማህበረሰብ ክፍልን ያማከለ የባንክ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑንም ቺፍ ኦፊሰሩ አውስተዋል።
በውይይት መርሃ ግብሩ የኮርፖሬት ባንኪንግ ቺፍ ኦፊሰር አቶ ሳኅለሚካኤል መኮነን፣ የደንበኞች ግንኙነት መምሪያ ዳይሬክተር አቶ መሠረት አሰፋ፣ የምስራቅ አዲስ አበባ ዲስትሪክት ዳይሬክተር አቶ ሚኪያስ ክ/ማርያም፣ የዓለምአቀፍ የባንክ አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ እስክንድር ዳባ፣ ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ ሱሌማን አብደላ እንዲሁም የድሬዳዋ አካባቢ ማስተባበሪያ ቢሮ ኃላፊ አቶ ካሳሁን ኩሴን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል።
ባንኩ የሚሰጣቸውን አገልግሎቶች ከደንበኞች ጋር የሚያስተዋውቅበት ግሎባል ቱር በቀጣይም በተለያዩ ከተሞች እንደሚካሄድ ይጠበቃል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ
ለጋራ ስኬታችን!