
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ በተጠናቀቀው የሒሳብ ዓመት በሁሉም የመለኪያ መስፈርቶች የሚበረታታ ውጤት ማስመዝገቡን የባንኩ ዋና ስራ አስፈፃሚ ዶ.ር ተስፋዬ ቦሩ ተናገሩ።
ዋና ስራ አስፈፃሚው ይኸን ያሉት ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ የ2024/25 የሒሳብ ዓመት አፈፃፀም በገመገመበት እና የ2025/26 የሒሳብ ዓመት ዕቅድ ላይ ሐምሌ 28 ቀን 2017 ዓ.ም በስካይላይት ሆቴል ውይይት ባካሄደበት ወቅት ነው።
በተጠናቀቀው የሂሳብ ዓመት ተለዋዋጭ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያዎች መደረጋቸውን ያወሱት ዶ.ር ተስፋዬ በተለዋዋጭ ሂደት ውስጥ የአሰራር ማሸሻያ በማድረግ፣ አሉታዊ አሰራሮችን በመቅረፍ እና አወንታዊ ሁኔታዎችን በአግባቡ መጠቀማችን አመርቂ ውጤት እንድናስመዘግብ አስችሎናል ብለዋል።
የተከፈለ ካፒታልን በተመለከተ እንድናሟላ ከተሰጠን የጊዜ ገደብ አስቀድመን አምስት ቢሊዮን ብር የተከፈለ ካፒታል ማዝመዝገብ መቻሉም በውይይቱ ወቅት ተገልጿል።
በመድረኩ የቅርንጫፍ ስራ አስኪያጆች የተጠናቀቀውን የሒሳብ ዓመት አስመልክተው መስተካከል አለባቸው እንዲሁም ተጠናክረው ቢቀጥሉ ያሏቸውን ሀሳቦች አቅረበዋል።
ለተጠየቁት ሀሳብ እና አስተያየት ምላሽ የሰጡት የባንኩ ከፍተኛ ኃላፊዎች የተጀመረውን የሂሳብ ዓመት ከዕቅድ በላይ ለመፈፀም ያልተቆጠበ ክትትል እና ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል።



የውጭ ምንዛሬ ግኝት፣ የሀብት አሰባሰብ፣ የብድር አሰጣጥ እና አመላለስ፣ የቴክኖሎጅ ግኝቶችን መጠቀም፣ የዲጅታል ባንክ ስርዓት አጠናክሮ ማስቀጠል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ትኩረት ተሰጥቶ ከተሰራባቸው ተግባራት መካከል መሆናቸው ተነግሯል።
በ2025/26 የሒሳብ ዓመት ከዚህ ቀደም ይስተዋሉ የነበሩ ክፍተቶችን በመቅረፍ እና ጥንካሬዎችን በማስቀጠል በየዓመቱ እየጨመረ የመጠውን ውጤታማ ስራ ዘንድሮም አጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባ ተገልጿል።
በ2024/25 የሒሳብ ዓመት ባንኩ ላስመዘገቡ አመርቂ የስራ አፈፃፀም የቦርድ አመራር አባላት፣ ከፍተኛ የባንኩ ኃላፊዎች፣ ሰራተኞች፣ ባለድርሻ አካላት እና ደንበኞች መሆናቸውን የገለፁት ዋና ስራ አስፈፃሚው ለተገኘው ውጤት የበኩላቸውን ሚና ለተወጡ አካላት ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
በመጨረሻም የግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ዋና ስራ አስፈፃሚ ዶ.ር ተስፍዬ ቦሩ በተጀመረው የሒሳብ ዓመት መከወን ይገባል ያሏቸውን ተግባራት እና የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎችን ሰጥተዋል።
በስብሰባው የባንኩ ዋና ስራ አስፈፃሚ፣ ቺፍ ኦፊሰሮች፣ ዳይሬክተሮች፣ ዲቪዥን ማናጀሮች እና የቅርንጫፍ ስራ አስኪያጆች ተሳትፈዋል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ
ለጋራ ስኬታችን!