
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ሴት ሰራተኞችን በማብቃት ወደ አመራርነት ማምጣት የሚያስችል የስልጠናና የትምህርት መርሃ ግብር መስከረም 10 ቀን 2018 ዓ.ም በስካይላይት ሆቴል በይፋ አስጀምሯል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ሰራተኞቹን ለማብቃት ዘርፈ ብዙ ስልጠናወችንና ትምህርቶችን በመስጠት ላይ እንደሚገኝ የሰው ሀብት አስተዳደር ዳይሬክተር አቶ ዳንኤል ማሞ በአደረጉት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር አመላክተዋል።
በተያዘው የሂሳብ ዓመት 120 ሴት ሰራተኞችን በልዩ ሁኔታ ለማሰልጠንና ለማስተማር ዕቅድ መያዙን የገለፁት አቶ ዳንኤል ስልጠናው በተከታታይ አራት አመታት ከ450 በላይ ሴት ሰራተኞችን ለማብቃት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ሰራተኞቹ ብቁ እና ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ያልተቆጠበ ክትትል እና ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ያወሱት አቶ ዳንኤል በቅርብ ጊዜ ውስጥ እስከ 3ኛ ዲግሪ ወይም ፒ.ኤች.ዲ አስተምሮ ለማስመረቅ በዝግጅት ላይ መሆኑን ተናግረዋል።
ሴቶችን ወደ አመራር ሰጭነት ለማምጣት እና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ከምን ጊዜውም በላይ ትኩረት አድርጎ እየሰራ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የፋይናንስና ሰፖርት ሰርቪስ ቺፍ ኦፊሰር አቶ ዳሳ ጎቤ ናቸው።




በአመራር ላይ ያሉ ሴቶችን ብቃታቸውን ማሳደግ እና አመራር ያልሆኑ ሰራተኞችን ወደ አመራር እንዲመጡ ድጋፍ ማድረግ የመርሀ ግብሩ ዓላማ መሆኑን አቶ ዳሳ ጎቤ ተናግረዋል።
ያላቸውን ልምድና ክህሎት ለተሳታፊዎች ያካፈሉት የግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ የዳይሬክተሮች ቦርድ የስራ አመራር አባል ወ/ሮ አዲስ ዘለቀ፤ ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ሴቶችን ለማብቃት እያደረገ ያለውን ጥረት በሙሉ አቅም ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆናቸውን ተናግረዋል።
የያንግ ኢንተርፕርነር ፕሮግራም ዋና ስራ አስፈፃሚ ወ/ሮ አስቴር አስፈው በበኩላቸው ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ብቁ እና ተወዳዳሪ የሆኑ ሰራተኞች ለማፍራት እያደረገ ያለው ጥረት የሚደገፍ እና የሚበረታታ መሆኑን ገልፀዋል።
በመርሃ ግብሩ የዲጂታል ባንኪንግ ዳይሬክተር ወ/ሮ መቅደስ በቀለ፣ የኢንጂነሪንግ ክፍል ኃላፊ ወ/ሮ አደይ አበበ፣ የሰው አሴት ስራ አስፈፃሚ ወ/ሮ እቴነሽ አሰፍ እንዲሁም የፕሮግረስ ማርኬቲንግ ሶሊዩሽንስ ስራ አስፈፃሚ ወ/ሮ ትርሲት ፈለቀ “መሪነት በተግባር” በሚል ርዕስ የፓናል ውይይት አካሂደዋል።
በፓናል ውይይቱ በሀገር አቀፍ ደረጃም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሴቶችን በአመራር ሰጭነት በብዛት እንደማይስተዋል የገለፁት የውይይቱ ተሳታፊዎች ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ሴቶች ላይ ትኩረት አድርጎ መስራቱ በፋይናንስ ኢንዱስትሪው የሚስተዋለውን ክፍተት መሙላት እንደሚችል ያላቸውን እምነት ገልፀዋል።
በቀጣይ በሚሰጠው ስልጠናና ትምህርት የሚሳተፍ የባንኩ ሴት ሰራተኞች በተካሄደው የመክፈቻ መርሀ ግብር ደስተኞች መሆናቸውን ገልፀው ባንኩ ያዘጋጀውን ስልጠና በአግባቡ ተከታትለው ብቁ እና ተወዳዳሪ ሰራተኛ በመሆን ባንኩ ራዕዩን እውን እንዲያደርግ የበኩላቸውን ኃላፊነት እንደሚወጡ ገልፀዋል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ3 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ሰራተኞች የተለያዩ ስልጠናዎችን የወሰዱ ሲሆን ከ70 በላይ ሰራተኞች ደግሞ አጠቃላይ በባንክ አሰራር ዙሪያ ለስድስት ወራት አሰልጥኖ ማስመረቁ ይታወቃል።
በስልጠና ማስጀመሪያው መርሃ ግብር የግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ የቦርድ ስራ አመራር አባል የሆኑት ወ/ሮ አዲስ ዘለቀ፣ ወ/ሮ ሀና ወንድም አገኝ እና ካፒቴን ሊዲያ ቴወድሮስ፣ የባንኩ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ
ለጋራ ስኬታችን!