
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ የመተሳሰብ ተምሳሌት የሆነውን የረመዳን ፆም ምክንያት በማድረግ በድሬዳዋ ከተማ ለሚገኙ ደንበኞች የኢፍጣር መርሃ-ግብር መጋቢት 8 ቀን 2018 ዓ.ም አካሂዷል።
በዝግጅቱ ላይ የባንኩ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣ በድሬዳዋ ከተማ የሚገኙ ደንበኞች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እና የከተማዋ መጅሊስ ተወካዮች ታድመዋል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ከንግድ እንቅስቃሴው ባሻገር ማህበራዊና ሃይማኖታዊ እሴቶችን ማክበርና ከደንበኞቹ ጋር ያለውን መልካም ትስስር ይበልጥ እንዲጠነክር ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየተከወኑ መሆኑን የማርኬቲንግና ኮምዩኒኬሽንስ ዳይሬክተር አቶ ቢኒያም ፍቃዱ በመርሃ ግብሩ ወቅት ባደረጉት ንግግር አመላክተዋል።
የዛሬውን ጨምሮ በአዲስ አበባና በተለያዩ ከተሞች ያካሄድነው የኢፍጣር ፕሮግራም ከደንበኞቻችን ጋር ያለንን ቤተሰባዊ ትስስር የምናድስበትና ለሰጡን እምነት ምስጋና የምናቀርብበት ነው ያሉት አቶ ቢኒያም፤ ባንካችን ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎቱን (ግሎባል ሐቂቃ) ተደራሽነት ይበልጥ ለማስፋት በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል።






ረመዳን የሰላም፣ የፍቅርና የልግስና ወር መሆኑን የጠቀሱት የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር መጅሊስ ተወካይ እና የመስጅዶችና አቁዋፍ ኃላፊ ሼህ አብደላ አሜ፤ ለተደረገው ኢፍጣር ምስጋናቸውን አቅርበው ተቋማት ማህበረሰቡን በሚጠቅሙ ተግባራት ላይ መሰማራታቸው በህዝቦች መካከል ያለውን አብሮነት እንደሚያጠናክር በአፅንኦት ተናግረዋል።
በኢፍጣር ፕሮግራሙ ላይ የታደሙ የባንኩ ደንበኞች፣ ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ለደንበኞቹ የሰጠውን ክብርና ያሳየውን መልካም ግንኙነት አድንቀዋል።
በከተማዋ ለሚንቀሳቀሱ ነጋዴዎችና ግለሰቦች ምቹ የሆኑ የባንክ አገልግሎቶችን እያቀረበ እንደሚገኝ የጠቀሱት በኢፍጣር መርሃ ግብሩ የታደሙ ደንበኞች ይኸን መሰል ዝግጅት በባንኩና በደንበኛው መካከል ያለውን ግልፅነትና መተማመን ይበልጥ እንደሚያጠናክረው ተናግረዋል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ በአዲስ አበባና በተለያዩ ከተሞች 1447ኛውን የረመዳን ፆም ምክንያት በማድረግ በኢኮኖሚ ዝቅ ላሉ ሰዎች የተለያዩ የአስቤዛ ድጋፎችንና ለደንበኞች ደግሞ በጋራ የሚያፈጥሩበትን መድረክ እያዘጋጀ ይገኛል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ
ለጋራ ስኬታችን!