
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ከኢትዮጵያ ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (EEC) ጋር ያለውን የስራ ትብብር አጠናክሮ ማስቀጠል የሚያስችል ውይይት ጥር 21 ቀን 2018 ዓ.ም አከናውኗል።
የዛሬው ውይይት ከዚህ በፊት በአዲስ አበባና በተለያዩ ከተሞች ግሎባል ቱር በሚል መሪ ቃል እየተካሄደ የሚገኘውን የደንበኞችን የስራ እንቅስቃሴ የመጎብኘት መርሃ ግብር አንዱ አካል ነው።
በውይይቱ ባንኩ እና ኮርፖሬሽኑ ለጋራ ስኬት በጋራ መስራት በሚቻልባቸው ምቹ ሁኔታዎች ዙሪያ ጥልቅ ውይይት ተካሂዷል።
መንግስታዊ ከሆኑ እና ካልሆኑ ተቋማት ጋር ለጋራ ስኬት በትብብር መስራት የግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ አንዱ እሴት መሆኑን የገለፁት የባንኩ ከፍተኛ ኃላፊዎች ከኢትዮጵያ ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ጋር ያለን የስራ ትብብርም ይህንኑ ያረጋግጣል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ላለፉት 70 ዓመታት በበርካታ የስራ ዘርፎች ላይ የዲዛይን፣ የቁጥጥር እና የግንባታ ስራዎችን ሲያከናውን መቆየቱን የገለፁት የኮርፖሬሽኑ ዋና ስራ አስፈፃሚ ኢንጂነር ሽመልስ እሸቱ ከቅርብ ጊዜ ጀምሮ ከሀገር ውጪም የተለያዩ ስራዎችን እየሰራ መሆኑን አመላክተዋል።



ባንኩ ኮርፖሬሽኑ ለሚያከናውናቸው የተለያዩ ፕሮጀክቶች የሚያደርገውን የፋይናንስ ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥልም ዋና ስራ አስፈፃሚው ጠይቀዋል።
ኮርፖሬሽኑ በሀገሪቱ የልማት ፕሮጀክቶች ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ የገለፁት የባንኩ ቦርዶች እና ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች የተጀመሩ ስራዎችን በጥራት እና በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ እንዲጠናቀቁ ባንኩ የሚያደርገውን ሁለንተናዊ ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አሳውቀዋል።
ሁለቱ ተቋማት ከዚህ በፊት በጋራ ሲሰሩ ያጋጠሙ እንከኖችን እንዴት መፍታት እንደሚቻል እንዲሁም ጠንካራ ሁኔታዎችን ይበልጥ አጠናክሮ ማስቀጠል በሚቻልበት ሁኔታ ዙሪያ ውይይት የተካሄደ ሲሆን ሁለቱም ተቋማት ያለውን የስራ ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር ቁርጠኞች መሆናቸውን ገልፀዋል።
በውይይት መርሃ ግብሩ የግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ዮሴፍ ጌታቸው፣ የባንኩ ዋና ስራ አስፈፃሚ ዶ/ር ተስፋዬ ቦሩ፣ የቦርድ አባላት እና ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል።
ግሎባል ቱር በሚል መሪ ቃል የባንኩን ደንበኞች የስራ እንቅስቃሴ የመጎብኘት መርሃ ግብር በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ይጠበቃል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ
ለጋራ ስኬታችን!