
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ግሎባል ቱር በሚል መሪ ቃል ከደንበኞች ጋር የሚያደርገውን የውይይት መድረክ በጅማ ከተማ ከሚገኙ ደንበኞች ጋር መስከረም 15 ቀን 2018 ዓ.ም በዶሎሎ ሆቴል አካሂዷል።
በውይይት መርሃ ግብሩ የባንኩን የስራ እንቅስቃሴ አስመልክተው የመወያያ ሀሳብ ያቀረቡት የደንበኞች ግንኙነት መምሪያ ዳይሬክተር አቶ መሰረት አሰፋ ባንኩ በበርካታ መለኪያዎች አመርቂ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን ገልፀዋል።
በቀረበው የመወያያ ሰነድ መሰረት በማድረግ ሀሳባቸውን የሰነዘሩት የውይይቱ ተሳታፊዎች ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ የደንበኞችን ሀሳብ እና አስተያየት ለማድመጥ እንዲሁም የመፍትሔ ሀሳብ ለመስጠት ይኸን መሰል መድረክ ማዘጋጀቱ የሚበረታታ መሆኑን ተናግረዋል።
የባንኩ የተደራሽነት አድማስ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየሰፋ መምጣቱን የገለፁት የውይይቱ ተሳታፊዎች በቀጣይም ከዚህ የበለጠ መሰራት እንዳለበት በተለይ በጅማ እና አካባቢው ተጨማሪ ቅርንጫፎች ተከፍተው አገልግሎት እንዲሰጡ ጠይቀዋል።
ለተነሱ ሀሳብ እና አስተያየቶች ምላሽ የሰጡት የኮርፖሬት ባንኪንግ ቺፍ ኦፊሰር አቶ ሳኅለሚካኤል መኮንን ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ለደንበኞቻችን የማያዳግም መፍትሄ ለመስጠት ተከታታይ ውይይቶች እየተካሄዱ መሆኑን ገልፀዋል።



ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ በመላ የሀገሪቱ ክፍል ቅርንጫፎችን ከፍቶ አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝ የገለፁት የባንኩ ኃላፊዎች በቀጣይም አስፈላጊ በሆኑ አካባቢዎች ጥናት በማድረግ አገልግሎት ለመስጠት ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል።
የግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ መሪ ቃል ለጋራ ስኬታችን የሚል እንደሆነ ያወሱት የባንኩ ከፍተኛ ኃላፊዎች የደንበኞቻችን ስኬት የባንኩም ስኬት በመሆኑ ደንበኞቻችን ስኬታማ እንዲሆኑ ባንኩ ያልተቆጠበ ክትትል እና ድጋፍ እያደረገ መሆኑን በመድረኩ ተናግረዋል።
በውይይት መድረኩ የግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ ቺፍ ኮርፖሬት ባንኪንግ ኦፊሰር አቶ ሳኅለሚካኤል መኮንን፣ የባንኩ ዳይሬክተሮች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
ግሎባል ቱር በሚል መሪ ቃል በተለያዩ ከተሞች እየተካሄደ የሚገኘው የውይይት መድረክ በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ይጠበቃል።
ግሎባል ባንክ ኢትዮጵያ
ለጋራ ስኬታችን!